Logo
News Photo

የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ለምዕራብ ሐረርጌ ዞን ትምህርት ቤቶች የኮምፒተር ድጋፍ አደረገ

የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ምዕራብ ሐረርጌ ዞን ስር ለሚገኙ ትምህርት ቤቶች የሚውሉ 50 አዳዲስ ኮምፒተሮችን ድጋፍ አደረገ።

የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ኡባህ አደም 6.7 ሚሊየን ብር ግምት ያላቸውን 50 አዳዲስ ኮምፒተሮች ለምዕራብ ሐረርጌ ዞን አመራሮች እንዲሁም ድጋፉ ለተደረገላቸው የትምህርት ቤት ዳይሬክተሮች አስረክበዋል።

ዶ/ር ኡባህ አደም በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት ´´የዲጂታል ኢትዮጲያ 2030 እቅዶች እንዲሳኩ እንዲሁም ተማሪዎች በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሳሉ መሰረታዊ የዲጂታል እውቀት እንዲኖራቸው የትምህርት ቤቶችን የኮምፒተር ቤተ-ሙከራዎች ማደራጀት አስፈላጊ ነው´´ ብለዋል፡፡  

ለምዕራብ ሐረርጌ ዞን የተደረገው ድጋፍ በዞኑ ስር የሚገኙ ትምህርት ቤቶችን የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ለማሟላት ያለመ ነው ያሉት ዶ/ር ኡባህ ድጋፉ ተማሪዎች በተግባር የተደገፈ የዲጂታል እውቀት እንዲቀስሙና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረት የሚያግዝ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡

የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የምርምር እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ም/ፕሬዝዳንት ዶ/ር ተማም አወል በበኩላቸው ድጋፉ የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የዲጂታል ልማት ስራዎች ላይ የሚያደርገውን ጉልህ አበርክቶ ይበልጥ የሚያጠናክር ነው = ብለዋል፡፡

የምስራቅ ሐረርጌ ዞን አስተዳዳሪ ወ/ሮ ኢክራም ጠሃ በበኩላቸው የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ያደረገው ድጋፍ በዞኑ ስር የሚገኙ ትምህርት ቤቶችን በእጅጉ ከማገዙም በላይ መንግስት በ2018 ዓ/ም የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ የመውጫ ፈተና በተመረጡ ሁለተኛ ደረጃ ት/ርት ቤቶች ለመስጠት ያቀደው እቅድ እንዲሳካ ያግዛል ብለዋል፡፡

Share This News

Comment